Monday, January 5, 2026

የሕይወት ሜዳ እና ሰማያዊው VAR

 በአረንጓዴው ሳር ላይ በሚደረገው የእግር ኳስ ጨዋታ፣ የሰው ዓይን ሊያያቸው የማይችሉ ስህተቶችን ለመለየትና ፍትሕን ለማረጋገጥ VAR (Video Assistant Referee) እንደ ዋና ዳኛ ረዳት ሆኖ ይሠራል፤ ስሜትን ይገታል፣ የታመነ ውሳኔንም ይሰጣል። ይኽ ቴክኖሎጂ በስፖርቱ ዓለም አዲስ ክስተት ቢሆንም፣ የሰው ልጅ ሕይወት ግን ከተፈጠረ ጀምሮ በማያንቀላፋና ሁሉን በሚያይ መለኮታዊ "VAR" ሥር ነው። ሕይወት ዝም ብሎ የሚፈስ ወንዝ ሳይሆን፣ እያንዳንዱ እንቅስቃሴው፣ አሳቡና ድብቅ ምኞቱ በሰማያዊው ማያ ላይ የሚመዘገብበት ታላቅ የፍርድ አደባባይ ነው።


በሕይወት ጨዋታ ውስጥ የምናስቆጥራቸው "ጎሎች" ወይም ስኬቶች ሁሉ በሰዎች ዘንድ እውቅና ሊያገኙ ይችላሉ፤ ነገር ግን እውነተኛው ዳኛ እግዚአብሔር ወደ ኋላ ተመልሶ (Review) የሚያየው የጎሉን መቆጠር ብቻ ሳይሆን፣ አኳኋኑንና የልባችንን ቅንነት ነው። መጽሐፍ ቅዱስ በሮሜ 2፥16 ላይ “ይህም እግዚአብሔር በኢየሱስ ክርስቶስ እኔ በወንጌል እንዳስተማርሁ በሰው ዘንድ የተሰወረውን በሚፈርድበት ቀን” በማለት እንደሚናገር፣ በሰው ዓይን የተሸሸገው ተንኮል፣ በጨለማ የተደረገው በደልና ማንም ያላየው "Offside" ሁሉ በዚያ ሰማያዊ ስክሪን ላይ በግልጽ ይታያል። እግዚአብሔር እንደ ሰው ፊት አይቶ ሳይሆን፤ እንደ ቃሉ ሕግና እንደ ልብ ንጽሕና ይፈርዳል።

ከዚህም በላይ፣ በኳስ ሜዳ ላይ አንድ ተጫዋች ሕግ ጥሶ ሲገኝ በVAR ታይቶ ከጨዋታ እንደሚወገድ ሁሉ፣ እኛም በሕይወት ሩጫችን ከመለኮታዊው መስመር ወጥተን የምናደርገው ሩጫ ዋጋ የለውም። በ2ኛ ጢሞቴዎስ 2፥5 ላይ እንደተጻፈ፣ “ደግሞም በጨዋታ የሚታገል ማንም ቢሆን፥ እንደሚገባ አድርጎ ባይታገል፥ የድሉን አክሊል አያገኝም”። በሕይወታችን የምናተርፈው ትርፍና የምናከማቸው ሀብት በመለኮታዊው መመዘኛ ሲታይ "Double Touch" ወይም በሐሰት የተገኘ ከሆነ፣ በመጨረሻው የፍርድ ፊሽካ ወቅት ውድቅ መሆኑ አይቀሬ ነው። እያንዳንዱ ንግግራችንና ድርጊታችን በሰማይ መዝገብ "Pending Decision" በሚል ጥንቃቄ ተመዝግቦ ይቆያል።

ይሁን እንጂ የሰማዩ VAR ከምድራዊው የሚለይበት አንድ አስደናቂ ሚስጥር አለው፤ እርሱም የንስሐ ዕድል ነው። በኳስ ሜዳ VAR ጥፋትን አጋልጦ ለቅጣት ሲዳርግ፣ የእግዚአብሔር ቃል ግን ስህተታችንን አሳይቶ ለንስሐና ለዕርቅ ይጋብዘናል። በ1ኛ ዮሐንስ 1፥9 መሠረት፣ ኃጢአታችንን ብንናዘዝ እርሱ ይቅር ሊለንና ጨዋታችንን በንጽሕና እንድንቀጥል ሊያደርገን የታመነ ነው። ይኽ ሰማያዊ ግምገማ እኛን ለመቅጣት ብቻ ሳይሆን፣ ወደ ቀጥተኛው መንገድ እንድንመለስና የሕይወትን ዋንጫ እንድንበላ የሚረዳን መለኮታዊ ረዳታችን ነው።

ሕይወታችን በሰዎች ፊት የምናሳየው ድራማ ሳይሆን በእግዚአብሔር ፊት የምንኖረው እውነት ነው። በስታዲየም ውስጥ ያሉት በሰላሳና በአርባ ካሜራዎች የታገዙ ዳኞች ሊሳሳቱ ይችላሉ፤ ሁሉን የሚመለከተው የፈጣሪ ዓይን ግን መቼም አይሳሳትም። ስለዚህ ዛሬ በሕይወት ሜዳ ላይ ስንሮጥ፣ በስተመጨረሻ "Decision is Goal" ወይም "Decision is Valid" የሚል የጽድቅ ውሳኔ እንድናገኝ፣ በቅንነት፣ በሕግና በፍቅር መጫወት ይኖርብናል። ምክንያቱም እውነተኛው ድል የሚለካው በሰው ጭብጨባ ሳይሆን፣ በታላቁ ዳኛ ፍጹም ፍርድ ነውና።

ይድረስ፣ ከበለስ በታች ሳለህ ለታየኸው!

https://t.me/anidSew

No comments:

Post a Comment