በጥልቁ የሰው ልጅ ታሪክ ውስጥ፣ ከጥንት እስከ ዛሬ ድረስ ሰው የማይረካ ጥማቱን የሚያረካበትን "ሕይወት"፣ ከጨለማ የሚወጣበትን "እውነት" እና ወደ ሰላም ወደብ የሚደርስበትን "መንገድ" ፍለጋ ዓለምን ሲዞር ኖሯል። በታሪክ መድረክ ላይ የተነሱ ብዙ መምህራን 'መንገዱን ላሳያችሁ' አሉ፣ ብዙ ፈላስፋዎችም 'እውነትን ልንገራችሁ' ብለው ሞከሩ፣ ብዙ መሪዎችም 'ሕይወታችሁን ላቅልላችሁ' በማለት ቃል ገቡ፤ ነገር ግን ማንም ቢሆን 'መንገዱ እኔ ነኝ' ለማለት የደፈረ የለም። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን በዮሐንስ ወንጌል 14፥6 ላይ "እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ፤ በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም" ብሎ ሲናገር፣ እርሱ ጠቋሚ ብቻ ሳይሆን የጥያቄዎቻችን ሁሉ መድረሻ መሆኑን አበሰረ። ይኽ ቃል በሰውና በእግዚአብሔር መካከል ተበጥሶ የነበረውን ግንኙነት የሚቀጥል መለኮታዊ ድልድይ ነው።
ኢየሱስ ክርስቶስ "መንገድ" ሲሆን፣ የሰው ልጅ በገዛ ጥረቱ ሊደርስበት ያልቻለውን የእግዚአብሔርን ጽድቅና ቅድስና የምንወርስበት ብቸኛ መተላለፊያ ሆነ። እኛ ደክመንና ተሳስተን በጠፋንበት በዚያ የኃጢአት በረሃ ውስጥ፣ እርሱ መጥቶ የሰማዩን ደጅ ከፈተልን። እርሱ "እውነት" ሲሆን ደግሞ፣ ዓለም በሐሰትና በከንቱ ፍልስፍና የሸፈነችውን የመኖር ትርጉም ገለጠልን። እውነት በክርስቶስ ዘንድ ሐሳብ ብቻ አይደለችም፤ እውነት በክርስቶስ ዘንድ የሚታይና የሚዳሰስ ማንነት ነው። እርሱን ማወቅ ማለት ከጥርጣሬ ባርነት ነፃ መውጣትና በጽኑ መሠረት ላይ መቆም ነው። "ሕይወት" ሲሆን ደግሞ፣ በሞት ጽላሎት ውስጥ ለነበረው የሰው ልጅ የዘላለም ተስፋን ሰጠ። ይኽም ሕይወት የልብ ትርታ ብቻ ሳይሆን፣ ከፈጣሪ ጋር ለዘላለም የመኖር መለኮታዊ ጸጋ ነው።
በመጨረሻም፣ ይኽ ቃል የክርስትናን ብቸኝነትና ፍጹምነት ያረጋግጣል። ክርስቶስ "ከመንገዶች አንዱ" ሳይሆን "ብቸኛው መንገድ" ነው፤ "ከእውነቶች አንዱ" ሳይሆን "ፍጹሙ እውነት" ነው፤ "ከሕይወት አማራጮች አንዱ" ሳይሆን "የሕይወት ምንጭ" ነው። ወደ አብ ለመድረስ ከእርሱ በቀር ሌላ በር፣ ሌላ ስም፣ ሌላም ዋስትና የለም። ዛሬም በዚኽ መንገድ ላይ የምንራመድ፣ በዚኽ እውነት የምንመራና በዚኽ ሕይወት የምንኖር ሁሉ ከቶ አንጠፋም። የዓለም መጨናነቅና የኑሮ ውጥረት ቢበረታም፣ መንገዱ ክርስቶስ የሆነለት ሰው መድረሻው የታወቀ ነው፤ እርሱም ሰማያዊውና ዘላለማዊው የእግዚአብሔር እቅፍ ነው።
መንገዳችን ክርስቶስ፣ እውነታችን ደግሞ ቃሉ፣ ሕይወታችንም መንፈሱ ይሁን። ከመንገዱ ሳንወጣ፣ በእውነቱ ታጥበን፣ በሕይወቱ ለምልመን ለዘላለም እንድንኖር ጸጋው ይርዳን።
የጌታ ኢየሱስ ጸጋ ከመንፈሳችሁ ጋር ይሁን!
ከ . . . እስከአሁን ድረስ እግዚአብሔር ረድቶናል!
https://t.me/anidSew
No comments:
Post a Comment