Monday, January 5, 2026

ነገ የሚባል የለም፤ ያለው ዛሬ ብቻ ነው!

"ነገ" የሚባለው ረጅም ጉዞ፣ ሩቅ የሚታይ አድማስ ሳይሆን በዛሬው ማህፀን ውስጥ የሚረገዝ ፅንስ ነው። ብዙዎች የነገውን ወርቃማ ፀሐይ በናፍቆት እየጠበቁ፣ በእጃቸው ያለውን የዛሬውን ፋኖስ ያጠፋሉ። በሚያምር የታሪክ ማማ ላይ ለመቀመጥ ያልማሉ፤ ነገር ግን ያ ማማ የሚቆምበትን የመሠረት ድንጋይ ዛሬ ለመቅረጽ ይፈራሉ፤ ይታከታሉ።


መጽሐፍ ቅዱስ “አንተ ታካች፥ ወደ ገብረ ጕንዳን ሂድ፥ መንገድዋንም ተመልክተህ ጠቢብ ሁን” (ምሳ. 6፥6) እንደሚል፣ ታላቅነት የሚገኘው በታታሪነት ውስጥ ነው። ማወቅ ያለብህ ታላቅ እውነት ግን ይኽ ነው፣ ታሪክ የሚጻፈው በታላላቅ መድረኮች ጩኸት ሳይሆን፣ ማንም በማያይህ በዛሬው የብቻነት ትግልህና በታማኝነትህ ውስጥ ነው። ጌታችን በቃሉ “አንተ በጎ ታማኝም ባሪያ፤ በጥቂቱ ታምነሃል፥ በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ” (ማቴ. 25፥21) እንዳለ፣ የነገው የክብር ዙፋን የሚገኘው በዛሬው ታማኝነት ልክ ነው።

ዛሬ የምታፈሰው ላብ፣ ነገ የምትጠጣው ጣፋጭ ውሃ ይሆናል። ዛሬ በመከራ የምትቀብረው ዘር፣ ነገ በትውልድ ጥላ የሚሆን ታላቅ ዛፍ ሆኖ ይበቅላል። “በልቅሶ የሚዘሩ በደስታ ይለቅማሉ። በሄዱ ጊዜ፥ ዘራቸውን ተሸክመው እያለቀሱ ተሰማሩ፤ በተመለሱ ጊዜ ግን ነዶአቸውን ተሸክመው ደስ እያላቸው ይመጣሉ” (መዝ. 126፥5-6)።

ስለዚህ የነገን ታሪክ ለመጻፍ ብዕር አትፈልግ፤ ይልቅስ የዛሬን ሰዓት እንደ መጥረቢያ ተጠቀምባት።

የዛሬው ድካምህ፣ የነገው ኩራትህ ነው!

No comments:

Post a Comment