'አውቃለሁ' በሚል ትዕቢት ውስጥ የታሰረ ልብ፣ አዲስ እውነትን ለመቀበልም ሆነ የቆመበትን ስህተት ለመረዳት ይቸገራል። 'ለብዙ ዓመታት አስተምሬያለሁ' ወይም 'አባቶቼ ሰብከውታል' የሚለው መመኪያ፣ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ዕውቀትን ሳይሆን ሃይማኖታዊ ኩራትን ነው የሚገልጸው። ይሁን እንጂ፣ መጽሐፍ ቅዱስን ማወቅ ማለት ቁጥሩንና ምዕራፉን መጥቀስ ሳይሆን፣ የመስቀሉን ቃል በተግባር መኖር ነው። ብዙዎች ስለ ክርስቶስ ቢሰብኩም፣ ክርስቶስን ግን በሕይወታቸው አያውቁትም፤ አንዳንዴም የረሱት ይመስላል።
ዛሬ ላይ 'ድህነት የክርስትና መገለጫ አይደለም' የሚሉ ድምፆች ሲበዙ መስማት ልብን ይሰብራል። ይኽ አባባል የመጽሐፍ ቅዱስን ገጽ ገልጦ ያላነበበ፣ ያነበበ እንኳ ቢሆን ከምድራዊ ነገር ጋር የተጋባ፣ የመስቀሉን ምስጢር ያልተረዳና የአባቶችን የጽናት ታሪክ የዘነጋ ትውልድ ጩኸት ነው። ክርስትና የሚለካው በባንክ ደብተር ሳይሆን በልብ ቅድስና ነው፤ ክርስትና የሚለካው በምቾት ሳይሆን በመከራ ውስጥ በሚገኝ ጽናት ነው። ድህነትን የውድቀት ምልክት አድርገው የሚሰብኩ ሰዎች፣ ጌታቸው ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ 'ራሱን የሚያሳርፍበት ማሳረፊያ የሌለው' ድሃ ሆኖ መመላለሱን እንዴት ዘነጉት? ደሞ'ኮ ጌታ 'ደሃ' አልነበረም ሲሉም አይሸማቀቁም።
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም ሲመጣ የተወለደው በቤተ መንግሥት ሳይሆን በከብቶች በረት ውስጥ ነው። የሰማይና የምድር ጌታ ሆኖ ሳለ፣ ለእኛ ሲል ድሃ ሆነ። ሐዋርያው ጳውሎስም "እስከዚህ ሰዓት ድረስ እንራባለን፥ እንጠማለን፥ እንራቆታለን... ሲሰድቡን እንመርቃለን" (1ቆሮ. 4፥11-12) በማለት የሐዋርያነት ሕይወት ከምድራዊ ቅንጦት የራቀ መሆኑን መስክሯል። ድህነት የክርስትና መገለጫ ካልሆነ፣ ታዲያ ሐዋርያቱ 'ክርስቲያን አልነበሩም' ሊባሉ ነው? ክርስትና በምድራዊ ጥሪት ሳይሆን በሰማያዊ ተስፋ የተሞላ ሕይወት ነው።
መጽሐፍ ቅዱስ "በእምነት ባለ ጠጎች እንዲሆኑ . . . እግዚአብሔር የዚህን ዓለም ድሆች አልመረጠምንም?" (ያዕ. 2፥5) ይላል። እውነተኛ ባለጸግነት በእግዚአብሔር ዘንድ ባለጸጋ መሆን ነው። ዛሬ ድህነትን የሚጸየፉ ሰዎች፣ ነፍሳቸው በኃጢአት መዝለሏንና በመንፈሳዊ ድህነት ውስጥ መውደቃቸውን ማየት ተስኗቸዋል። እግዚአብሔር ሰውን የሚመዝነው ባለው ንብረት ሳይሆን በውስጣዊ ማንነቱ ነው። በአልዓዛር ቁስልና ድህነት ውስጥ ያለ ክብር፣ በባለጸጋው ሰውዬ ቅንጦት ውስጥ ካለው ውርደት ይበልጣል።
ክርስትና ''ተመችቶኝ ልኑር'' የሚሉ ሰዎች መንገድ ሳይሆን "መስቀሉን ተሸክመው የሚከተሉ" ጀግኖች ጉዞ ነው። ዛሬ "ድህነት አይገባኝም" የሚለው ትውልድ፣ ነገ "መከራም አይገባኝም" ማለቱ አይቀርም። ይኽ ደግሞ ክርስቶስን ያለ መስቀሉ መፈለግ ነው። ሰማዕታት የሞቱት፣ አባቶች ጫካና በረሃ የወደቁት ለምድራዊ ሀብት አልነበረም፤ ይልቁንም "ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል?" በማለት በድህነትና በራብ ውስጥ ሆነው ለዘላለማዊው ክብር ስለቆሙ ነው።
ሀብታም መሆን ኃጢአት አይደለም፣ ድሃ መሆንም ጽድቅ አይደለም። ነገር ግን 'ድህነት የክርስትና መገለጫ አይደለም' ብሎ ድሆችን ማሳቀቅና ክርስትናን ከገንዘብ ጋር ማያያዝ ግን ታላቅ ስህተት ነው። ክርስትና ባለን ነገር የመርካት፣ በሌለን ነገር ደግሞ እግዚአብሔርን የመማጸን ጥበብ ነው። ወዳጄ ሆይ! በምድራዊ ድህነት ውስጥ ሆነህ ሰማያዊው ንጉሥ ካንተ ጋር ከሆነ አንተ ከሁሉ በላይ ባለጸጋ ነህ። ድምፅህ ከሰባኪያን ጩኸት ይልቅ የጌታን ቃል ይስማ፤ እርሱ "በምድር ሀብት አታከማቹ" ብሎናልና! ልባችሁ በምድራዊ ሀብት ሳይሆን በሰማያዊ ጸጋ ይሙላ! በድህነት ውስጥ ክብርን፣ በችግር ውስጥ ምስጋናን የሚሰጥ አምላክ ያጽናችሁ! በክርስቶስ ዘንድ ባለጸጋ ሆናችሁ እንድትገኙ ጸጋው ይርዳን!
የጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ ከመንፈሳችሁ ጋር ይሁን!
Tuesday, January 6, 2026
ክርስትና በመስቀል እንጂ 'በኪስ' አይለካም፤ በቃ አይለካም!
https://t.me/anidSew
Subscribe to:
Post Comments (Atom)
No comments:
Post a Comment