በታሪክ ማህደር ውስጥ ካሉ ክስተቶች ሁሉ እጅግ ታላቅና አስደንጋጭ፣ ነገር ግን ለሚጠባበቁት እጅግ ናፍቆት የሆነው ያ ቀን ይመጣል። ዓለም በልማዷ በምትታመስበት፣ የሰው ልጆች በምድራዊ ጭንቀትና በትዕቢት በታወሩበት በዚያ ድንገተኛ ሰዓት፣ ሰማይ እንደ ጥቅልል ይከፈታል። ያን ጊዜ የሰው ልጅ ታሪክ አቅጣጫውን ለዘላለም ይለውጣል። የሰማይ መከፈት ብቻ ሳይሆን፣ ለእውነተኞቹ የዘላለም ንጋት የሚጀምርበት፣ የሞትና የህመም ጥላ የሚያበቃበት ያ የክብር ቀን ነው።
ያ ቅጽበት ልክ እንደ ዓይን ጥቅሻ ፈጣን ነው። የመላእክት አለቃ ድምፅና የእግዚአብሔር መለከት ሲነፋ፣ ምድር ከዚህ ቀደም ሰምታው የማታውቀውን ድምፅ ትሰማለች። ያ ድምፅ ለዓለም ፍርድ፣ ለቅዱሳን ግን የሰርግ ጥሪ ነው። በክርስቶስ ሆነው ያንቀላፉት ቅዱሳን መቃብራቸውን ሰብረው በክብር ይነሳሉ። የማይበሰብሰውና የማይሞተው አዲሱ ማንነታቸው ከምድር አፈር ውስጥ እንደ ጸሐይ ብርሃን ፈንጥቆ ይወጣል። ሞት ድል ተመትቶ፣ መቃብር ባዶውን ቀርቶ፣ ቅዱሳን ከጌታቸው ጋር ለመገናኘት ወደ ሰማይ ይተኮሳሉ።
ከዚያም እኛ በሕይወት የምንኖረው፣ ድካምና መከራ የሰለቸን፣ በናፍቆት አይኖቻችን የፈዘዙት፣ በቅጽበት እንለወጣለን። ይህ የሚሞተው ስጋችን የማይሞተውን ይለብሳል። የምድር ስበት ሊይዘን አይችልም፤ የአየር ክልል ጋሬጣ ሊያግደን አይችልም። ልክ ብረት ወደ ማግኔት እንደሚሳብ፣ እኛም ወደ ወደደንንና ነፍሳችንን በደሙ ወደ ዋጀው ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ እንሳባለን። በአየር ላይ ከጌታ ጋር ስንገናኝ፣ ያኔ የእንባ ዘመን ያበቃል፤ የጋሬጣና የእሾህ ምድር ወደ ኋላችን ትቀራለች።
በደመና መካከል የምናየው ፊቱ እንደ ጸሐይ የሚበራውን፣ እጆቹ የፍቅሩን ምልክት፣ የችንካሩን ጠባሳ፣ የያዙትን፣ የነፍሳችንን እረኛ ነው። ያኔ "ጌታ ሆይ እስከመቼ?" ብለን የጠየቅነው ጥያቄ በክብር መልስ ያገኛል። ፍጹም በሆነ ሰላም፣ በማያልቅ ደስታና በከበረ ዝማሬ እንከበባለን። ሙሽራይቱ ቤተክርስቲያን ከሙሽራው ክርስቶስ ጋር ለዘላለም ትዋሀዳለች። ያ ቀን የድካማችን ማብቂያ፣ የሩጫችን ግብና የፍቅራችን ፍጻሜ ነው።
እስከዚያው ግን ልባችን "ጌታ ኢየሱስ ሆይ ና!" እያለ ይቃትታል። በምድር ላይ ስንመላለስ እንደ እንግዳና እንደ መጻተኛ ነው፤ ምክንያቱም ቤታችን እዚህ አይደለምና። ዓይኖቻችን ወደ ሰማይ ተተክለዋል፣ ጆሮዎቻችን የመለከቱን ድምፅ ለመስማት ተዘጋጅተዋል። ያ የተባረከ ተስፋችን፣ የክብር አክሊላችንና የነፍሳችን መልሕቅ እርሱ ኢየሱስ ክርስቶስ በክብር ተመልሶ ይመጣል። መምጣቱም እጅግ ቅርብ ነው!
🙏🙏ከፀሐይ መውጫ እስከ መጥለቂያዋ ድረስ ስምህ ይባረክ፤ የነፍሳችን እረኛና የዘላለም ንጉሥ ሆይ! ከምድር ስበትና ከዓለም ድካም ነጥቀህ ወደ ቅድስናህ ፊት እስከምትወስደን ድረስ በናፍቆት እንጠባበቅሃለን፤ ማራናታ፣ ጌታ ኢየሱስ ሆይ በቶሎ፣ በፍጥነት ና!🙏🙏
No comments:
Post a Comment