የኢየሱስ ክርስቶስ ሊቀ ካህንነት ከሰው ልጆች ሥርዓትና ከሕግ በላይ የሆነ፣ በመለኮታዊ መሐላ የጸና የዘላለም አገልግሎት ነው። እርሱ እንደ አሮን ሥርዓት ሳይሆን፣ የማይጠፋ ሕይወት ኃይል ባለው "እንደ መልከ ጼዴቅ ሥርዓት" ለዘላለም ካህን ሆኖ ተሹሟል። ይህ አገልግሎት በምድራዊ መቅደስ ሳይሆን፣ በእውነተኛይቱ ድንኳን በሰማያት በእግዚአብሔር ቀኝ የሚከናወን ነው። ዕብራውያን 7፡25 እንደሚለው፣ እርሱ ስለ እነርሱ ሊያማልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል።
ክርስቶስ ሊቀ ካህን የሆነው በሌላ ፍጡር ደም ሳይሆን፣ በገዛ ደሙ አንዴ ወደ ቅድስተ ቅዱሳን በመግባት የዘላለምን ቤዛነት አግኝቶልናል። እርሱ መሥዋዕቱም፣ መሥዋዕቱን አቅራቢውም ነው። እንደ ብሉይ ኪዳን ካህናት በየቀኑ መሥዋዕት ማቅረብ አያስፈልገውም፤ ምክንያቱም ራሱን አንድ ጊዜ አሳልፎ በመስጠት የኃጢአትን ግድግዳ ደምስሷል። ይህ አገልግሎት ለሰው ልጅ የእርቅ መንገድን የከፈተና ወደ ጸጋው ዙፋን በድፍረት እንድንቀርብ ያደረገ ታላቅ የምሥራች ነው።
ክርስቶስን የመሥዋዕታችን ሊቀ ካህን፣ የድካማችን ረዳትና የነፍሳችን ጠባቂ ነው። ክርስቶስ አማላጅ ብቻ ሳይሆን፣ ወደ አብ የምንቀርብበት ብቸኛው "በር" ነው። እርሱ ብቻ የአብን ስውር ምስጢር የሚያውቅና ወደ አብ የሚያደርስ ነው። ክርስቶስ በሰማያዊው መሠዊያ ላይ ጸሎታችንን የሚያሳርግ፣ በቅድስናውም እኛን የሚቀድስ ዘላለማዊ መካከለኛ ነው።
የክርስቶስ ሊቀ ካህንነት ዛሬ ላይ ላለን ክርስቲያኖችም ትልቅ መጽናኛ ነው። እርሱ በድካማችን ሊራራልን የማይችል አይደለም፤ ነገር ግን በነገር ሁሉ ከኃጢአት በቀር እንደ እኛ የተፈተነ፣ ስለሆነ፣ ለሚፈተኑት ሊረዳቸውና ሊራራላቸው ይችላል (ዕብ. 4፥15)። በሰማይ ያለን ጠበቃና ሊቀ ካህን ዛሬም ስለ እኛ ይቆማል፤ የኃጢአታችንን ክስ በደሙ ዋጋ ይሽራል። የእርሱ አገልግሎት በሞት አይገታም፤ ምክንያቱም እርሱ ለዘላለም ሕያው ነው። አማኞች በዚህ ታላቅ ሊቀ ካህን ተመርኩዘን ወደ ጸጋው ዙፋን እንቀርባለን። እርሱ በሰማያዊው መቅደስ ለእኛ ስፍራን ያዘጋጃል፣ በመንፈስ ቅዱስ አማካኝነትም ከእግዚአብሔር ጋር ያለንን አንድነት ያጸናል። የክርስቶስ ሊቀ ካህንነት የክርስትና እምነት እምብርትና የዘላለም ሕይወት ዋስትናችን ነው።
የጌታ ሰላም ይብዛላችሁ!
No comments:
Post a Comment