Monday, January 5, 2026

💪ለእናንተ ነው . . . ለእነርሱ አይደለም!❤️

 ልባችሁ ለጠፉት የሚራራ፣ እጆቻችሁ የተሰበሩትን ለመጠገን የሚዘረጋ፣ ከእግዚአብሔር ለሚመጣላችሁ ጥሪ መንፈሳችሁ የሚቀጣጠል፤ ይኽ ለእናንተ ነው።


የእግዚአብሔርን ሳይሆን የራሳቸውን መንግስት ለመመስረትና ለመገንባት የሚፋጠኑ 'መሪዎች'፤ የዝና ጥማት የሚያሰክራቸው፣ የገንዘብ ፍቅር ቃጠሎ የሚያነዳቸው፣ ሕዝቡን የራሳቸውን ግብ ለመፈጸም መጠቀሚ መሣሪያቸው ያደረጉ ብዙ 'አገልጋዮች' ነን የሚሉትን 'እነእንትናን' አይታችኋል። የአገልግሎትን ትክክለኛ ድርጊት የጣሰ ተግባር ነው። ወይ የአገልግሎትን ጥሪ መካድ ነው።፤ ወይ ደግሞ ጠሪው እግዚአብሔር ያልሆነበት 'የአገልግሎት ሥራ' ነው።

ቀረብ ብላችሁ ስሙኝ፤ በደንብ አድምጡኝ። የእነርሱ ውድቀት፣ በተሳሳተ መንገድ ላይ መሆናቸው የእናንተን ጥሪ አይገልጸውም። የእነርሱ ነገሮችን compromise የማድረግ ድርጊታቸው የእናንተን ጸጋ cancel አያደርገውም። (ያው አንዳንድ እንግሊዘኛ ቃላትን ልጠቀም ብዬ ነው፤ 'እነእንትና' ጸሐፊው 'የተማረ' ይመስላቸዋልና ነው፤ እናንተ ደግሞ አሁን ይኼ እንግሊዘኛ መሆኑ ነው? እንዳትሉ። ሰፍሬ ለክቼ በእነርሱ ልክ ነው ያስቀመጥኩት፤ እነዚህን ቃላቶች 'እነእንትና' በጣም ይወዷቸዋል)

ዓለም 'በቤተክርስቲያን' መድረኮች ላይ ያቆመቻቸው በቂ CEOs አሏት። በጣም ብዙ ዝነኛና ታዋቂ የሆኑ ራሳቸውን 'እረኞች' በማድረግ የሚያታልሉ celebrities አሏት። ዓለም የራባት፤ ቤተክርስቲያንም የናፈቀችው እውነተኛ አገልጋይ ነው። የፍቅር ዘማቾች፤ ራሳቸውን የከዱ የክርስቶስ አምባሳደሮች፣ የኢየሱስ ወኪሎች፤ አድነኝ እያለ ለሚጮኽ ድምጽ ፈጣን ምላሽን የሚሰጡ ተወርዋሪ ከዋክብት። እኔን የማያውቁ፣ ሁልጊዜ ንግግራቸው እርሱ (ኢየሱስ ክርስቶስ) የሆነላቸው። ዓለም እኚኽ ያስፈልጓታል። ለዓለም የምታስፈልጉ፣ እግዚአብሔርን የምትወዱት እናንተ አስታውሱ . . .

👉 ጥሪያችሁ ከሰው ሳይሆን ከእግዚአብሔር ነው።
የእናንተን 'ዕጣ ፈንታ' ቁልፍ የያዘ አንድም ፓስተር የለም። የእናንተ ሹመት፣ ማረጋገጫችሁ በጸጥታ 'ከሆነ ቦታ' ከጠራችሁ ከእርሱ የመጣ ነው። ሳሙኤል በሌሊት በእግዚአብሔር እንጂ በኤሊ አልተጠራም። ዳዊት የተቀባው በሜዳ ላይ ነው እንጂ በቤተ መንግሥት አልነበረም። ሰው እጁን ሊጭንባችሁ ይችላል ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ ነው የሚለያችሁ። የተዘጋው የሰው በር የተከፈተውን የእግዚአብሔርን በር እንድትጠራጠሩ እንዲያደርጋችሁ አትፍቀዱለት።

👉 ተምሳሴታችሁ፣ አርአያችሁ፣ ምሳሌያችሁ ክርስቶስ እንጂ የሆነ 'ታዋቂ' ሰው አይደለም። ኢየሱስን ተመልከቱ። ሕንጻ አልነበረውም፤ የማስታወቂያ ቡድንም ሆነ የፖለቲካ ተጽእኖ የሚያደርግበት አልነበረውም። እግሩ አቧራማ፣ የደከመ አካል፣ ለሰዎች ደግሞ የተሰበረ፣ የሚያዝን፣ የሚራራ ልብ ነበረው። የብዙዎችን እግር አጠበ። ለምጻሞችን ነካ።  ከኃጢአተኞች ጋር በላ። መሪነትን አገልጋይነት፣ ታላቅነት ደግሞ ትህትና እንደሆነ ገልጿል። ትዕቢተኞችን ለማየት ስትፈተኑ ወደ መስቀል ተመለስ።  ያ የእናንተ ሞዴላችሁ ነው። ያ የእናንተ ኃይላችሁ ነው።

👉 ልባችሁን ጠብቁ፤ እልከኛ አታድርጉት። በግብዝ ሰዎችና በድርጊቶቻቸው ማዘን ትክክል ቢሆንም ያ ሀዘን ወደ ቂምና ምሬት አይለወጥ። ያላችሁን ስሜት በንፅህና ጠብቁ፣ ልባችሁን ለስላሳ የሆነና ለፍቅር የተከፈተ አድርጉት። መራራ እረኛ መራራ መንጋ ብቻ ነው የሚመራው። ህመማችሁ ርህራሄን እንጂ ትችታችሁን አያቀጣጥል።

👉 የዝግጅት ጊዜህ የተቀደሰ ነው። ይህ ትግል፣ ይህ በሰው ችላ የመባል ስሜትን እግዚአብሔር የሚያየው ነው። በእናንተ ውስጥ ምን አይነት ነገር እየፈጠረ እንደሆነ እናንተው ታውቃላችሁ። እግዚአብሔር ግን በእርሱ ብቻ እንድትመኩ እያስተማራችሁ ነው። የመድረክ ፍላጎትን ገፎ በእናንተ ውስጥ እርሱ የሚጠቀምበትን ባህሪ እየገነባ ነው። እግዚአብሔር በእናንተ ውስጥ በትኛውም የትዕቢት ማዕበል የማይናወጥ የትሕትና መሠረትን እየገነባ ነው።

👉 'በተለየ መንፈስ' ተነሱ። ሌሎቹ እንዲሆኑ የምትፈልጉትን መሪ፤ እንዲኖራችሁ የምትመኙት መሪ እናንተው ሁኑት። የሚያስፈራና የሚያስፈራራ ሳይሆን ኃይልን የምትሰጡ ሁኑ። የሌሎችን ስኬት የምታከብሩ ሁኑ እንጂ በሌሎች ስኬት ስጋት አይሰማችሁ። ማይክራፎኑን የምትሰጡ፣ መጪውን ትውልድ የምትመክሩ፣ የሚዲያ ሳይሆን የአገልጋዮችን legacy የምትገነቡ ሁኑ። እንደ በርናባስ የጳውሎስን አቅም አይቶ ለእርሱ ጥብቅና እንደቆመለት ሁኑ። መንግሥቱ የሚባዛው በልግስና እንጂ በስግብግብነት አይደለም።

ለእነርሱ👹 ተቀብዬ እስክመለስ . . .  ለእናንተ የተቀበልኩትን እነሆኝ ብያለሁ።

የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ ከመንፈሳችሁ ጋር ይሁን!

ተጻፈ ከአንድ ሰው በብዙ ሰዎች በኩል ይደርስ ዘንድ ለአንድ ሰው!

No comments:

Post a Comment