Tuesday, October 14, 2025

ከክርስቶስ ጋር ህብረት

 ክርስትና ዋና ክፍል በቀላሉ የምንስማማባቸው እምነቶች ዝርዝር ወይም መከተል ያለብን 'ሃይማኖታዊ' ልማዶች አይደሉም። ህያውና በሆነ፣ በሚለውጥ ህብረት ውስጥ ከክርስቶስ ጋር መሆን ነው። የኃጢያት ይቅርታን ማግኘት በራሱ ውድ የሆነ ነገር ቢሆንም መዳን ግን ከዚህ በላይ ነው፤ ከእግዚአብሔር ልጅ ጋር አንድ የሆንበት እውነታ ነው።  ጳውሎስ ይህንን እውነት ሲጽፍ “ማንም በክርስቶስ ቢሆን አዲስ ፍጥረት ነው፤ አሮጌው ነገር አልፎአል፤ እነሆ፥ አዲስ ሆኖአል” (2ቆሮ. 5፡17) ሲል ጽፏል። በዚህ አንድነት፣ በክርስቶስ መስቀል፣ ሞት፣ መቃብር፣ ትንሣኤ እና ዕርገት ተሳታፊ ሆነናል። ከክርስቶስ ጋር ተሰቅላችኋል፣ ከክርስቶስ ጋር ሞታችኋል፣ ከክርስቶስ ጋር ተቀብራችኋል፣ ከክርስቶስ ጋር ሕይወትን አግኝታችኋል፣ ከክርስቶስ ጋር ተነስታችኋል፣ ከክርስቶስ ጋር . . . የተካፈልናቸው ሌሎች በረከቶች የክርስትና መለዮ ናቸው። እናም በዚህ መከራው መከራችን፤ ሞቱ ሞታችን፤ መቀበሩ መቀበራችን፤ ሕይወቱ ሕይወታችን፤ ትንሳኤው ትንሳኤያችን፤ ክብሩ ክብራች ሆኗል። ምን ቸገረኽ! በቃ፣ የእርሱ ታሪክ ታሪካችን ሆኗል።


በዚህ እውነታ ላይ ሁለንተናችንን ሰጥተን ስናሰላስል መፅናናትን የምናገኝ ሲሆን። ፈጽሞ ልንተው በማንችልበት ኅብረት ውስጥ መሆናችንን እንረዳለን፤ ክርስቶስ ሁልጊዜ ከእኛ ጋር እንዲሁም በእኛ ውስጥ እንደሆነ እንገነዘባለን። ይኽ ደግሞ መጽናናትን ያመጣል፣ ዕረፍትን ይሰጣል፣ የነፍስ ሰላምን ይጠብቃል። ከክርስቶስ ጋር ኅብረት እንዳለን በሚገልጽ እውነት ላይ ማሰላሰል መጽናናትን የሚሰጠን ቢሆንም፣ በሌላ መንገድ ደግሞ ሕይወታችን ምን መምሰል እንዳለበት የሚሞግተንም ጭምር ነው። ከእርሱ ጋር ከተባበርን ትዳራችን፣ ጓደኞቻችን፣ ስራችን እና አሳባችን እንኳን ሳይቀር የእርሱን ህልውና የሚያንፀባርቅ መሆን አለበት። በዚህም ምክንያት "ክርስቶስ በእኔ እንዳለ ሆኜ እየኖርኩ ነውን? ሌሎች የእርሱን ባህሪ በእኔ ውስጥ እያዩ ነውን?" በሚሉ ጥያቄዎች ይሞግተናል።

ከክርስቶስ ጋር ኅብረት ለሥነ-መለኮት መምህራንና ተማሪዎች ብቻ የተሰጠ ረቂቅ ትምህርት አይደለም።  የክርስትና ሕይወት የልብ ምት ነው። ሁሉንም ነገር የሚቀይር እውነት ነው። አሳቦቻችንን፣ አነጋገራችንን፣ አካሄዳችንን በቃ ሁሉን የሚቀይር ነው።

እውነተኛና ሕያው የሆነ እርሱ ወደጥልቅ መረዳት ውስጥ ይከተን ዘንድ፣ አብሮነቱ እስኪሰማን ድረስ ያሳርፈን ዘንድ፣ ጸጋውና ምህረቱ ይብዛልን!

No comments:

Post a Comment