በገሊላ አቧራማ መንገዶችን እየተራመደ፤ ለእግሩ ምቾት ሳር አንጠፉልኝ ሳይል በእነዚያ ኮረብቶች ላይ እየተመላለሰ የሰበከው ኢየሱስ እርሱ ሥጋ የሆነው ቃል ነው። እግዚአብሔር በሰዎች መካከል ሆነ። ለደከሙ ነፍሳት ሕይወትን ተረከ። ከዙፋኑ ሳይሆን ከዚሁ ከአንዲት መንደር መንገድ እምብርት ላይ ቆሞ በርኅራኄ ሰበከ። እርሱ የሆኑ ንድፈ ሐሳቦችን ሳይሆን እውነትን ሰበከ፤ የእውነተኛውን አምላክ ልብ ገለጠ። የተናገረው ቃል ሁሉ ጨለማን የሚያጋልጥ ብርሃን፣ እስራትን የበጣጠሰና ሰንሰለት የሰበረ ፍቅር፤ ሰዎችን ነፃ የሚያወጣ እውነትን ይዞ ነበር።
ያ ሰባኪው ኢየሱስ እንዲህ ብሎ ነበር “እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ፥ ወደ እኔ ኑ፥ እኔም አሳርፋችኋለሁ” (ማቴ. 11፥28) ይኽ የጥሪ ድምጽ ዛሬም ያለማቋረጥ ይሰማል። አንዴ የተነገረ፣ ለሁል ጊዜ የሚሰማ፤ ለጥቂቶች የተነገረ ለብዙዎች የተስተጋባ ጥሪ። አስባችሁታል፣ መልእክቱ' ኮ 'ወደ እኔ ኑ' ነው። ግንኙነትን የሚያስጀምር፣ መጠጊያን የሚያኖር፣ ዕረፍትን የሚሰጥ ጥሪ ነው። መሸሸጊያ ስፍራን የሚሰጥ ጥሪ ነው። ይኼ ሰባኪው ኢየሱስ ለከሳሾቹ ባሳየው በምሕረቱ፣ በእንባው እና በዝምታው የአብን ፊት ገለጠ። ከእግዚአብሔር ጋር መኖርን እንደ ሩቅ ተስፋ ሳይሆን ንስሐ ለሚገባ ልብ ሁሉ ሕያው የሆነ እውነታ አድርጎ ሰበከ።
ከሞቱና ከትንሳኤው በኋላ ግን ያ ይሰብክ የነበረ ድምጽ ራሱ የሚሰበክ መልእክት ሆነ። አሁን ሐዋርያቱ “መጥታችሁ እርሱን ስሙት” ብቻ አላሉም “በእርሱ እመኑ” እያሉ በጩኸት ተናገሩ። የተሰበከው ክርስቶስ ያው ኢየሱስ ነበር።
መስቀሉ የመቤዠት መልእክትን ለዘላለም የሚያስተጋባበት መድረክ ሆነ። ጳውሎስ “የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብካለን” (1ኛ ቆሮ. 1፥23) በማለት እርሱን ሰበከ። የተሰበከው ክርስቶስ ኃጢአትን ያሸነፈው አዳኝ፣ በመንፈሱ አሁን በእኛ የሚኖር ከሙታን መካከል የተነሳው ጌታ ነው። እርሱ ያው ኢየሱስ ነው። ከአሁን በኋላ በጊዜ ወይም በቦታ የተገደበ ሳይሆን በሚያምን ሁሉ ልብ ውስጥ የሚገኝ ነው።
ሰባኪውን ኢየሱስን ማወቅ በትህትና፣ በምህረት እና በንጽህና እንዴት መመላለስ እንዳለብን መማር ነው። የተሰበከውን ክርስቶስ ማመን ያለ ፍርሃት፣ በደስታ እና በኃይል በድል መኖር ነው። ሁለቱም በልባችን ሲዋሃዱ የወንጌልን ሙላት እናያለን፤ ጸጋ እና እውነት፣ ፍቅር እና ኃይል፣ መስቀል እና ትንሳኤ ወለል ብሎ ያታየናል።
“ኢየሱስ ክርስቶስ ትናንትና ዛሬ እስከ ለዘላለምም ያው ነው።” — ዕብ. 13፥8
No comments:
Post a Comment